ቅዱስ ፊልዾስ_ሐዋርያ: ኤላውትሮስ እና ለደናግል_አጥራስስ_ወዮና

✞✞✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞✞✞

✞✞✞ እንኩዋን ለቅዱስ ፊልዾስ_ሐዋርያ: ለቅዱስ ኤላውትሮስ እና ለደናግል_አጥራስስ_ወዮና ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞✞✞

” ቅዱስ ፊልዾስ_ሐዋርያ

 
እንደ አባቶቻችን ትርጉም ‘ፊልዾስ’ ማለት ‘#መፍቀሬ_አኃው#ወንድሞችን_የሚወድ‘ ማለት ሲሆን ከ12ቱ ቅዱሳን ሐዋርያት አንዱ ነው:: (ማቴ. 10:3) በዚህ ስም የሚጠራ ሐዋርያ ከ72ቱ አርድእት ውስጥ ነበር:: እርሱም ጃንደረባውን #ባኮስን ያጠመቀው ነው::
አንዳንዴ የ2ቱ ታሪክ ሲቀላቀል እንሰማለን:: ለሁሉም ይህኛው ቅዱስ ፊልዾስ ቁጥሩ ከ12ቱ ሐዋርያት ሆኖ ምሑራነ ኦሪት ከሚባሉትም አንዱ ነበር:: በወቅቱ ገማልያል የሚሉት ክቡርና ምሑረ ኦሪት በርካታ ምሑራነ ኦሪትን አፍርቶ ነበር::
እንደ ምሳሌም ቅዱሳኑን “ዻውሎስን: ኒቆዲሞስን: ናትናኤልን: እስጢፋኖስንና የዛሬውን ሐዋርያ ቅዱስ ፊልዾስን” መጥቀስ እንችላለን:: ቅዱስ ፊልዾስ ነገዱ ከእሥራኤል ሲሆን ተወልዶ ያደገው በቤተ ሳይዳ ነው:: ኦሪትን ተምሮ በመንገድ ዳር ቁጭ ብሎ ‘መሲሕ ቀረ’ እያለ ሲተክዝ ለስም አጠራሩ ጌትነት ይሁንና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እርሱ ደረሰ::
ትክ ብሎ አይቶት “ተከተለኝ” አለው:: (ዮሐ. 1:44) ቅዱስ ፊልዾስም ያለ ማመንታት: ሁሉን ትቶ በመንኖ ጥሪት ተከተለው:: በዚህ ዓይነት ጥሪ መድኃኒታችን ቅዱስ ማቴዎስንም ጠርቶታል:: (ማቴ. 9:9) ቅዱስ ፊልዾስ ጌታን ከተከተለ በሁዋላ ሥራ አልፈታም:: ወዲያውኑ ሒዶ ለናትናኤል (ቀናተኛው ስምዖን) ሰበከለት እንጂ::
“ሙሴ በኦሪት: ነቢያትም የተነበዩለትን መሲሕን አግኝቸዋለሁ” አለው:: ይሕ አነጋገሩም ምሑረ ኦሪት እንደ ነበር በእርግጥ ያሳያል:: (ዮሐ. 1:46) ቅዱስ ናትናኤልም ምሑር ነውና “ከናዝሬት ደግ እንዴት ይወጣል?” ቢለው ቅዱስ ፊልዾስም መልሶ “ነዐ ትርአይ-ታይ ዘንድ ና” አለው::
ናትናኤልም ሒዶ በጌታ አመነ:: ቅዱስ ፊልዾስ አገልጋይ እንደ መሆኑ መጠን በዮሐንስ ወንጌል ተደጋግሞ ስሙ ተጠቅሷል:: በተለይ ደግሞ ጌታ የ5 ገበያ ሕዝብን አበርክቶ ሲመግብ አስቀድሞ ጥያቄ ቀርቦለት ነበር:: እርሱ ግን “ጌታ ሆይ! የ200 ዲናር እንጀራ ብንገዛም አንዘልቀውም” ብሎ ነበር::
በሁዋላ ግን የጌታን ድንቅ ተአምር ተመለከተ:: (ዮሐ. 6:5) በተለይ ደግሞ በሐዋርያት አበው መካከል ለጌታ እንደ እንደራሴ ሆኖ ያገለግል እንደ ነበርም ተጠቅሷል:: ሰዎች ጌታን ማግኘት ሲፈልጉ እሱና እንድርያስን ያናግሩ ነበር:: (ዮሐ. 12:20) አንድ ጊዜ ግን እስካሁን ሊቃውንትን የምታስደምም ጥያቄ ጠይቆ ነበር::
አጠያየቁ ደግሞ ፍጹም የዋሕ እንደ ሆነ ያሳያል:: ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ባሕርይ አባቱ አብ እየነገራቸው ሳለ ቅዱስ ፊልዾስ ከመካከል ተነስቶ “እግዚኦ አርእነሁ ለአብ ወየአክለነ”: ልክ ወልድን በዐይኑ እንዳየ ሁሉ አብን ሊያይ ቸኩሎ “አቤቱ ስለ አብ የሰማነው ይበቃልና አሳየን” ብሎታል:: (ዮሐ. 14:8)
ጌታችን ግን “ዘርእየ ኪያየ ርዕዮ ለአብ-እኔን ያየ አብን አይቷል” (ዮሐ.14:9) ብሎ ምሥጢረ ባሕርዩን: አንድነቱን ሦስትነቱን አስረድቶታል:: ቅዱስ ፊልዾስም ጌታን እስከ ሕማሙ አገልግሎ: ቅድስት ትንሳኤውን አይቶ: ለ40 ቀናት መጽሐፈ ኪዳንን: ትምሕርተ ኅቡዓትን ተምሮ: ቅዱስ መንፈሱን ከ72 ልሳን ጋር ነስቶ ለስብከተ ወንጌል ወጥቷል::
ቅዱሳን ሐዋርያት ዓለምን በእጣ ሲካፈሉ ለእርሱ አፍራቅያ (አፍሪካ) ደርሳዋለች:: ስለዚህም በምድረ አፍሪካ ወንጌልን ከሰበኩ ሐዋርያት አንዱ ነው:: በአፍራቅያና በቀድሞው የኃምስቱ አሕጉር ግዛት ድንቅ ድንቅ ተአምራትን አድርጐ ብዙዎችን ወደ መንጋው (ወደ ክርስትና በረት) ቀላቀለ::
ለበርካታ ዓመታትም በተለያዩ የዓለም ክፍሎች እየተዘዋወረ ወንጌልን ሲሰብክ: ብርሃነ ክርስቶስን ሲያበራ: ነፍሳትንም ሲማርክ ቆየ:: ገድለ ሐዋርያት እንደሚለው የቅዱስ ፊልዾስ ፍጻሜው በሰማዕትነት እንደ ሆነ ቢታወቅም የትኛው ሃገር ውስጥ እንደ ሆነ መለየት አልተቻለም::
ዜናው ግን እንዲህ ነው:- በአንዲት ሃገር ውስጥ ገብቶ ሰበከ:: ብዙዎችንም አሳመነ:: ያላመኑት ግን ይዘው አሰቃዩት: ገረፉት:: “በክርስቶስ እመኑ እባካችሁ!” እያለ እየለመናቸው ዘቅዝቀው ሰቅለው ገደሉት::
ከዚያም በእሳት እናቃጥላለን ሲሉ ቅዱስ መልአክ ከእጃቸው ነጥቆ ወደ ኢየሩሳሌም ወሰደው:: በዚህ የደነገጡት ገዳዮቹ ለ3 ቀናት ጾሙ: ተማለሉ:: በዚህ ምክንያት የቅዱሱ ሥጋ ተመልሶላቸው: ገንዘው ቀብረውት በክርስቶስ አምነዋል::

” ቅዱስ ኤላውትሮስ ሰማዕት “

ቅዱሱ ሰማዕትና ቅድስት እናቱ (እንትያ ትባላለች) የዘመነ ሰማዕታት ፍሬዎች ናቸው:: ቅድስት እንትያ መልካም እናት ናትና ቅዱስ ኤላውትሮስን በሃይማኖት በሥርዓት አሳደገችው:: በ17 ዓመቱ ዲቁናን ተሾመ:: በ18 ዓመቱ ቅስና: በ20 ዓመቱ ደግሞ ዽዽስናን ተሾመ::
ያን ጊዜ ሃገራቸው ሮም የግፍ ቦታ ነበረችና የቅዱሱ ዜና ሕይወት: ብርሃንነቱ: ስብከቱ: ንጹሕ ሕይወቱ በሃገረ ገዢው ዘንድ ተሰማ:: አንዱን መኮንን ጠርቶ “ሒድ አምጣው” አለው::
መኮንኑ ሲደርስ ቅዱስ ኤላውትሮስ እየሰበከ ነበርና በጣዕመ ስብከቱ ተማርኮ ከነ ተከታዮቹ አምኖ በዚያው ቀረ:: አገረ ገዢውም ሌላ መኮንን ልኮ አስመጣውና ቅዱሱን “ለምን የተሰቀለውን ታመልካለህ?” አለው::
ቅዱሱም መልሶ “ማስተዋል የተሳነህ! ቢገባህ ኑሮ የተቀለው እኮ ለእኔና ለአንተ ነው” አለው:: ሞት ተፈርዶበት ቅዱሱን ብዙ አሰቃይተው እሥር ቤት ሲጥሉት ርግብ መጥታ መገበችው::
እግሩን ቸንክረው በመንገድ ላይ ሲጐትቱት መልአክ ወርዶ ፈታው:: ወደ በርሃም ወሰደው:: ከጊዜያት በሁዋላ እንደ ገና ይዘው አምጥተው: ብዙ አሰቃይተው በዚህች ዕለት: ከእናቱ ቅድስት እንትያ ጋር በጦር እየወጉ ገድለዋቸዋል::
ሊቃውንትም የሰማዕታቱንና የሐዋርያውን ተጋድሎ እያደነቁ እንዲህ ጸልየዋል:-
“ሰላም ለፊልዾስ ጽዑረ አባል በመቅሰፍት:
ወለኤላውትሮስ ርጉዝ በብልኃ ኩናት:
ምስለ እንትያ እባእ ኀበ ተርኅወ ገነት:
ያሩጸኒ መዓዛሆሙ ወጼናሆሙ ዕፍረት:
ለዝ ሐዋርያ ወለዝ ሰማዕት::” (አርኬ)

” ደናግል አጥራስስ ወዮና “

እሊህ ቡሩካት ሴት ወጣቶችም ምድራቸው ሮም ናት:: ቅድስት አጥራስስ የንጉሥ ልጅ ስትሆን ቅድስት ዮና ደግሞ የታላላቆች ልጅ ናት:: 2ቱ ቅዱሳት አንስት አይተዋወቁም ነበር:: ዮና ገና በልጅነቷ ክርስትናን አጥንታለች::
አጥራስስ ግን አባቷ ጣዖት አምላኪ በመሆኑ ቤት ሠርቶ: በወርቅ አንቆጥቁጦ ጣዖቶችን እንድታመልክ: ሰውም እንዳታይ አደረጋት:: እርሷ ግን ጣዖቱ እንደ ማይረባ ተመራምራ አውቃ ጣለችው::
“የማላውቅህ እውነተኛው አምላክ ተገለጽልኝ?” ስትልም ጸለየች:: ያን ጊዜ ቅዱስ መልአክ “ዮና የምትባል ሴት ታስተምርሽ” ስላላት አስፈልጋ አስመጣቻት:: ቅድስት ዮናም ክርስትናን ከጥንቱ ጀምራ አስተማረቻት::
2ቱ ቅዱሳት አብረው እየዋሉ: አብረው እያደሩ በጾምና በጸሎት ቢጠመዱ ድንግል ማርያም እመቤታችን ተገለጠችላቸው:: ከልጇ ዘንድ አቅርባም አስባረከቻቸው:: ይህ ሁሉ ሲሆን የቅድስት አጥራስስ አባት ንጉሡ በሃገር አልነበረም:: ሲመለስ ግን የሆነውን ሁሉ አወቀ::
ሕዝቡን ሰብስቦ በአንዲት ልጁ አጥራስስና በወዳጇ ዮና ላይ በእሳት እንዲሞቱ ፈረደባቸው:: እሳቱ ብዙ እጥፍ ነዶ ሕዝቡ ሲያለቅስላቸው 2ቱ ደናግል እርስ በርስ ተቃቅፈው ተሳሳሙ:: እየጸለዩም ወደ እሳቱ ተወረወሩ:: በዚያም ለፈጣሪያቸው ነፍሳቸውን ሰጡ:: እሳቱ ግን ልብሳቸውን እንኩዋ አላቀነበረውም::
አምላከ ቅዱሳን ስለ ወዳጆቹ ሲል ቸርነቱን: ምሕረቱን ይላክልን:: ከበረከታቸውም ይክፈለን::
ኅዳር 18 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ፊልዾስ ሐዋርያ (ከ12ቱ)
2.ቅዱስ ኤላውትሮስና እናቱ እንትያ (ሰማዕታት)
3.ቅዱሳት ደናግል አጥራስስ ወዮና (ሰማዕታት)
4.ቅዱስ አትናቴዎስ የዋሕ
ወርሐዊ በዓላት
1.አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ረባን
2.አቡነ አኖሬዎስ ዓቢይ
3.ማር ያዕቆብ ግብጻዊ
4.ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ (ከ72ቱ አርድእት)
“+ እኔንስ ብታውቁኝ አባቴን ደግሞ ባወቃችሁ ነበር:: ከአሁንም ጀምራችሁ ታውቁታላችሁ:: አይታችሁትማል አለው::
ፊልዾስ:- ‘ጌታ ሆይ! አብን አሳየንና ይበቃናል’ አለው:: ጌታ ኢየሱስም አለው:- ‘አንተ ፊልዾስ! ይህን ያህል ዘመን ከእናንተ ጋር ስኖር አታውቀኝምን? እኔን ያየ አብን አይቷል:: እንዴትስ አንተ አብን አሳየን ትላለህ? እኔ በአብ እንዳለሁ: አብም በእኔ እንዳለ አመታምንምን? +”+ (ዮሐ.14:7)

✞✞✞ ወስብሐት ለእግዚአብሔር ✞✞✞

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *