[ከተላላፊ በሽታ እንዴት እንጠበቅ?]

[ከተላላፊ በሽታ እንዴት እንጠበቅ?]

✍️ ከመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ
Megabe Haddis Rodas Tadese
❤️ በዓለም ላይ የሚነሡት አብዛኞቹ ተላላፊ በሽታዎች በቅዱስ መጽሐፍ የተከለከሉት እንስሳትን፣ አራዊትንና አዕዋፍን በመመገብ የመጡ እንደሆኑ፤ እነርሱንም በድናቸውን የነካ እንዴት በሽታው እንደሚተላለፍበት በሽታውን ለማስወገድ ምን ማድረግ እንደሚቻል የንጽሕናውን ሂደት ሁሉ በዝርዝር “መጽሐፍ ቅዱስና የሕክምና ሳይንስ” የሚለው መጽሐፌ ላይ በስፋትና በጥልቀት በጥናት የጻፍኩትን በመሆኑ መጽሐፉን አንባብያን እንዲያነቡ እየጋበዝኩ በዚያ ላይ ያልተካተቱ ተላላፊ በሽታዎች ሲከሠቱ አባቶቻችን ምን ያደርጉ እንደነበር በተወሰነ መልኩ በጥቂቱ ከዚህ በታች ጽፌያለሁ፡፡

(1) ካህናት በጸሎተ ዕጣን የማዕጠንት አግልግሎት መስጠት
❤️ ዳዊት አባታችን በመዝ 140፡2 ላይ “ተወከፍ ጸሎትየ ከመ ዕጣን በቅድሜከ” (ጸሎቴን በፊትህ እንደ ዕጣን ተቀበልልኝ) እንዳለ እግዚአብሔር ወዶ የሚቀበለው ጸሎተ ዕጣን ተላላፊ በሽታና መቅሠፍት በማራቅ ይታወቃል፡፡ ይኸውም በኃጢአታቸው ልዑል እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ሊቀሥፋቸው መቅሠፍቱ በጀመረና ሞት በመጣ ጊዜ ሙሴም አሮንን፦
✍️ “ጥናህን ውሰድ፥ ከመሠዊያውም ላይ እሳት አድርግበት፥ ዕጣንም ጨምርበት፥ ወደ ማኅበሩም ፈጥነህ ውሰደው አስተስርይላቸውም ከእግዚአብሔር ፊት ቍጣ ወጥቶአልና መቅሠፍት ጀምሮአል አለው፤ አሮንም ሙሴ እንደ ተናገረው ጥናውን ወስዶ ወደ ጉባኤው መካከል ሮጠ እነሆም፥ መቅሠፍቱ በሕዝቡ መካከል ጀምሮ ነበር ዕጣንም ጨመረ፥ ለሕዝቡም አስተሰረየላቸው፤ በሙታንና በሕያዋን መካከል ቆመ መቅሠፍቱም ተከለከለ” ይለናል፡፡ (ዘኁ 16:48-49)

❤️ ዛሬም በመልአኩ እጅ ይህ የቅዱሳን ካህናት የዕጣን ጸሎት የሚያርግና ግዳጅ የሚፈጽም በመሆኑ አበው ካህናት ልብሰ ተክህኖ ለብሰው ማዕጠንታቸውን ይዘው ሀገሪቱን በማጠን በጸሎተ ማዕጠንት መንፈሳዊ አደራቸውን ሊወጡ ይገባቸዋል፡፡ በኅዳር በሽታ ጊዜ ሕዝቡ ቆሻሻውን ሲያቃጥል ካህናት በማዕጠንት ባጠኑት ዕጣን ተላላፊው በሽታ ተገትቷል፡፡ ይኸውም ኅዳር ሲታጠን ተብሎ አሁን ድረስ በታሪክ ይነሣል፡፡

 በተለይ ጻድቁ አቡነ ሀብተ ማርያም ተላላፊ በሽታን በማዕጠንት ለማራቅ በዚህ ቃል ኪዳን የተሰጣቸው በመሆኑ የገዳሙ አባቶች በሀገራችን በተለያየ ስፍራ ተላላፊ በሽታ ሲመጣ የማዕጠንት አግልግሎት ሲሰጡ በሽታው እንደሚቆም ይታወቃልና መጠቀም የእኛ ድርሻ ነው፡፡

(2) በቅዱስ ሲኖዶስ የታወጀ ሀገር ዐቀፍ ምሕላን ዐውጆ በቤተ ክርስቲያን ተገኝቶ ወደ እግዚአብሔር መለመን፣ ማልቀስ፣ መማፀን

 በምሕላና በጸሎት ተላላፊ በሽታ እንደሚወገድ ራሱ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስን ሠርቶ ለጨረሰው ለሰሎሞን ቃል ኪዳንን እንዲህ ገብቶለታል፡-
✍️ “ዝናብ እንዳይወርድ ሰማያቱን ብዘጋ፥ ወይም ምድሪቱን ይበላ ዘንድ አንበጣን ባዝዘው፥ ወይም በሕዝብ ላይ ቸነፈር (ተላላፊ በሽታ) ብሰድድ በስሜ የተጠሩት ሕዝቤ ሰውነታቸውን አዋርደው ቢጸልዩ፥ ፊቴንም ቢፈልጉ፥ ከክፉ መንገዳቸውም ቢመለሱ፥ በሰማይ ሆኜ እሰማለሁ፥ ኃጢአታቸውንም ይቅር እላለሁ፥ ምድራቸውንም እፈውሳለሁ” ይላል (2ኛ ዜና 7፡13-14)፡፡

 በመሆኑም ጦርነት፣ ተላላፊ በሽታ የመሳሰለው እንዲህ ዓይነት መከራ ጥንት ሀገር ሲያጋጥማት ነገሥታቱ ከካህናት ጋር በመማከር በአንድ ላይ ምሕላና ጸሎት በሀገሩ ሁሉ ባሉ በየገዳማቱና በየአድባራቱ ሁሉ ሥዕለ ማርያም ምስለ ፍቁር ወልዳ ወጥቶ በዕንባ ይደርስ ነበር፡፡ ዛሬም ይህንን ታላቅ የምሕላ ጸሎት በማድረስ የሚታወቁት በአክሱምና በጎንደር ነውና በመላዋ ሀገሪቱ ሊሆን ይገባል፡፡

❤️ ለምሳሌ ያህል አሁን በመጣው የኮሮና ወረርሽኝ ከኃያላን ሀገራት ውስጥ የአሜሪካ መራሔ መንግሥት ፕሮዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እንኳን በትክክለኛው የፌስ ቡክ ገጻቸው ላይ፡- መጋቢት 6 እሑድ ሀገር ዐቀፍ የጸሎት ቀን እንዲሆን አውጄያለሁ፤ በታሪካችን ሁሉ በእንደዚህ ባለ ጊዜ እግዚአብሔር እንዲጠበቅን እንዲያጠነክረንም ወደ እግዚአብሔር እንመለከታለን የሚል መልዕክትን አስተላላፈው ነበር፡፡

 ቅዱስ ሲኖዶስም በነዚህ የፈተና ጊዜያት ሲከሰቱ የተነጣጠለ ምሕላ ሳይሆን ተፈጻሚነት ያለው የተጠናከረና በእንባና በንስሐ የሚፈጸም ሀገር ዐቀፍ ጸሎትና ምሕላ ማወጅና ማስፈጸም ይጠበቅበታል፡፡

(3) በሱባዔ ዘግተው የሚጸልዩ አባቶችን መጠየቅ

 እንደሚታወቀው ጌታችን በገዳመ ቆሮንቶስ ፵ መዓልትና ፵ ሌሊት የጾመውን አብነት አድርገው በገዳም ድምፀ አራዊቱን፣ ጸብዐ አጋንንቱን ታግሠው በጾም በጸሎት ከእግዚአብሔር ጋር በመገናኘት ከጽማዌ እስከ ከዊነ እሳት የደረሱ አባቶች ወዳሉብት ወደ ገዳም በመላክ መፍትሔውን ማወቅ ትልቅ ነገርና አባቶቻችን ሲያደርጉት የነበረው እውነት ነው፡፡

 ለምሳሌ ያህል ተላላፊ በሽታ ተከስቶ ሰባ ሺ እስራኤላውያንን ሲፈጃቸው ነቢዩ ጋድ የእግዚአብሔርን ቃል ጠይቆና ተረድቶ ዳዊት በኢያቡሳዊው በኦርና አውድማ ለእግዚአብሔር መሠዊያ ከሠራ መቅሠፍቱ እንደሚርቅ ስለነገረው፤ ዳዊትም የነቢዩን ቃል ሰምቶ ለእግዚአብሔር መሠዊያ ሠርቶ የሚቃጠልና የደኅንነትንም መሥዋዕት ባቀረበ ጊዜ እግዚአብሔርም ስለ አገሪቱ የተለመነውን ሰማ፥ መቅሠፍቱም ከእስራኤል ተከልክሏል (2ኛ ዜና 24፡1-25)፡፡

(4) በንሥሐ ሆኖ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን መቀበል

 ቅዱስ ቁርባንን መቀበል ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ እንደሚያድን ይልቁኑ ዘላላማዊ ሕይወትን እንደሚሰጥ ጌታችን በዮሐ 6፡49-50 ላይ:- “አባቶቻችሁ በምድረ በዳ መና በሉ ሞቱም፤ ሰው ከእርሱ በልቶ እንዳይሞት ከሰማይ አሁን የወረደ እንጀራ ይህ ነው” በማለት አስተምሮናል፡፡

 የበጉን ደም በበራቸው መቃን ያደረጉትን ሞተ በኩር ዐልፎ የግብጻውያንን በኩራት እንደገደለ ዛሬም ከኃጢአት የሚያነጻንን የክርስቶስን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን መቀበል ከመቅሠፍት ይጠብቃል፡፡ የሚያልፈው ዓለምን ሳይሆን የማያልፈውን ዓለምንም እንወርስበታለንና ንስሐ ገብተን ሥጋ ወደሙን እንቀበል፡፡

(5) በተላላፊ በሽታ ላይ ቃል ኪዳን ጌታ በገባላቸው በቅዱሳን ቃል ኪዳን መማፀን

 ልዑል እግዚአብሔር “ኪዳነ ተካየድኩ ምስለ ኅሩያንየ” (ከመረጥኳቸው ጋር ቃል ኪዳኔን አደረኩ) ብሎ እንደተናገረ በተላላፊ በሽታ ላይ ሥልጣን በሰጣቸው በመረጣቸው ቅዱሳን ቃል ኪዳን መማፀን ትልቁ መፍትሔ ነው፡፡

 በተለይ ታላቁ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስ ሰማዕትነትን በሚቀበልባት ዕለት “ወኀበ ተጸውዐ ስምየ በዛቲ መካን ኢይምጻዕ ሞተ ላሕም ወኢብድብድ በሰብዕ ወኢአባረ እክል ወሕፀተ ማይ” (ስሜ በሚጠራበት በዚያች ቦታ የከብት ዕልቂት፣ ተላላፊ በሽታ፣ በእህልም ላይ ድርቅ፣ የውሃም ማነስ አይምጣ) ብሎ ጸልዮ ጌታ ይሁንልህ ብሎ ቃል ኪዳንን ገብቶለታልና ገድሉን እየጸለዩ መማፀን ተገቢ ነው፡፡ ለታላቁ ጻድቅ ለአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስም ይህንን ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋልና በቃል ኪዳናቸው እንጠቀም፡፡

 ከዚህ ሁሉ ጋር ቅብዐ ቅዱሱ፣ ጠበሉ፣ መስቀሉ፣ ቅዱሳት ሥዕላት ሁሉ ከልዑል እግዚአብሔር የተሰጡን መንፈሳዊ ኃይላችን ናቸውና ከቸነፈር እንጠበቅባቸዋለንና የተሰጠንን መንፈሳዊ ጸጋ እንጠቀምባቸው፡፡
“ልዑል እግዚአብሔር ምድራችንን ይፈውስልን”
የቴሌግራም ቻናሌ https://t.me/joinchat/AAAAAFTyR7tztt08pN9U-w
ከመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *